በደቡብ ሱዳን ሁለት ኢትዮጵያውያን የሰላም አስከባሪዎች ተገደሉ - የተባበሩት መንግሥታት
በደቡብ ሱዳን በተሠማራው የተባበሩት መንግሥታት የሰላም ማስከበር ተልዕኮ አባላት የሆኑ ሁለት ኢትዮጵያውያን የሰላም አስከባሪዎች ሰኞ በማዕከላዊ ጆንግሌ ግዛት የቅኝት ሥራ በማካሄድ ላይ በነበሩበት ወቅት "ማንነታቸው ባልታወቁ አካላት" በተሰነዘረባቸው ድንገተኛ ጥቃት መገደላቸውን ተመድ በመግለጫው አስታውቋል። ዩኤንሚስ፤ "በጆንግሌይ ግዛት ወደ ፓጁት በማቅናት ላይ በነበረ የቅኝት ቡድን ላይ ማንነታቸው ባልታወቁ የታጠቁ አካላት የተሰነዘረውን ድንገተኛ ጥቃት በጽኑ ይኮንናል" ብሏል። በጥቃቱ ሦስት የሰላም አስከባሪዎች፣ ሁለት የደቡብ ሱዳን ፖሊሶች፣ ሁለት ሲቪል ሰራተኞችን ጨምሮ በርካታ ሰዎች ቆስለዋል ተብሏል። የዩኤንሚስ ኃላፊ አኒታ ኪኪ ጌሆ፤ “በደቡብ ሱዳን ሰላም ለማስፈን በሚሠሩ የዩኤንሚስ አባላት ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች በፍጹም ተቀባይነት የላቸውም” ብለዋል። የተመድ የደቡብ ሱዳን ተልዕኮ በ2003 ዓ.ም ከተቋቋመ ወዲህ፤ ከ160 በላይ የዩኤንኤሚስ አባላት ህይወታቸውን ማጣታቸውን የቅርብ ጊዜ የተባበሩት መንግሥታት መረጃዎች ያሳያሉ።