በደቡባዊና ሰሜን ምዕራብ ትግራይ አካባቢዎች
የድሮን ጥቃቶች መፈጸማቸው ተገለጸ ዛሬ ረፋዱ ላይ በደቡባዊ እና ሰሜን ምዕራብ የትግራይ አካባቢዎች የድሮን ጥቃቶች መፈጸማቸውን የክልሉ የዜና ምንጮች ዘገቡ። በደቡብ ትግራይ ዞን ራያ አዘቦ ወረዳ በተፈጸሙ ሁለት የድሮን ጥቃቶች በሲቪሎች ንብረትና በመስኖ እርሻ ልማት ላይ ጉዳት መድረሱን የዞኑ ባለሥልጣናት መናገራቸውን የክልሉ ቴሌቪዥን ጠቅሶ ዘግቧል። በተመሳሳይ በሰሜን ምዕራብ ዞን እንዳባጉና ወረዳ በተፈጸመው ጥቃት በሲቪሎች መኖሪያ ቤቶች ላይ ጉዳት መድረሱ ተመልክቷል። ለተፈጸሙት ጥቃቶች የትግራይ ክልል ባለሥልጣናት የፌደራል መንግሥቱን ተጠያቂ ያደረጉ ሲሆን፣ ጥቃቶቹ በደረሱባቸው አካባቢዎች በወቅቱ ወታደራዊ እንቅስቃሴ ስለመኖሩ ለጊዜው የተረጋገጠ ነገር የለም። ጉዳዩን በተመለከተ ከፌደራል መንግሥት በኩል የተሰጠ ምላሽ እስካሁን አልቀረበም።