ኬርያ ኢብራሂም ስለ ሕወሓት ውድቀትና
የትግራይ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ምን አሉ? የቀድሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ኬርያ ኢብራሂም ከኢቲቪ ትግርኛ ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ ሕገ ወጡ ሕወሓት በሙስና፣ በስልጣን ጥም እና በውስጥ ክፍፍል ሳቢያ ወደ ፈጣን መበስበስ ማምራቱን ገለጹ። ድርጅቱ ህዝባዊ ወገንተኝነቱን አጥቶ ስልጣንን ለግል ፍላጎት ማሳኪያ በማድረጉ እና ከሻዕቢያ ጋር አደገኛ ጥምረት በመፍጠሩ የትግራይን ህዝብ ለተጨማሪ ውድቀት እየዳረገው መሆኑን ጠቁመዋል። በጦርነቱ በተለይም ሴቶችና ህፃናት ማለቂያ የሌለው ስቃይ ማስተናገዳቸውን አንስተው፣ ህዝቡ መብቱ ተገፎ ለግል ጥቅም ሲባል ለጦርነት መማገዱን አውግዘዋል። አሁን ያለው ትውልድ በቃ ሊል እንደሚገባ ያሳሰቡት ወይዘሮ ኬርያ፣ የትግራይ ህልውና ከእንግዲህ በደም መፋሰስ ሳይሆን በህግ የበላይነት፣ በዕውቀት እና በሳይንሳዊ እድገት ሊረጋገጥ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። ሁሉም ወገን ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት፣ ቂም በቀልን በማስወገድ እና በክብ ጠረጴዛ ውይይት ልዩነቶችን መፍታት እንዳለበት ጥሪ አቅርበዋል።