የጨጓራ ህመም ተገቢዉን ህክምና ካላገኘ የምግብ መተላለፊያ ቱቦን በመዝጋት ለከፋ የጤና ችግር ሊያጋልጥ ይችላል ተባለ
የጨጓራ ህመምን በቤት ዉስጥ በተለያዩ መንገዶች ማከም አንዱ አማራጭ ቢሆንም ደረጃዉ ከፍ ሳይል ተገቢዉን የህክምና አገልግሎት ካላገኘ ለከፋ የጤና ችግር እንደሚያጋልጥ ተገልጿል።የጨጓራ ህመም ተገቢዉን የህክምና እርዳታ ካላገኘ እና ወደ መጨረሻዉ ደረጃ ከፍ ካለ ቁስለቱ እስከ መድማት ደርሶ ደም ማስመለስን ሊያስከትል ይችላል ። የጨጓራ ቁስለት በከፍተኛ ደረጃ ተባብሶ የጨጓራ ግድግዳን ሙሉ በሙሉ በመብሳት ቀዳዳ በሚፈጥርበት ወቅት በሆድ ዕቃ ውስጥ ከባድ ኢንፌክሽንን ስለሚያስከትል አስቸኳይ የሕክምና እርዳታ ማግኘት ተገቢ ነዉ ተብሏል ።በተጨማሪም ጨጓራ ከትንሹ አንጀት ጋር የሚገናኝበት ቦታ ላይ በተደጋጋሚ ጉዳት ሲደርስበት ቦታዉ ይጠብና የምግብ መተላለፊያ ቱቦን በመዝጋት ለከፋ የጤና ችግር ስለሚያጋልጥ ተገቢዉን የህክምና እገዛ ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ በየካቲት 12 ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ የዉስጥ ደዌ ስፔሻሊስት ዶክተር አምደመስቀል መርሻ ከብስራት ሬዲዮ ጋር ባደረጉት ቆይታ ተናግረዋል ። የህክምና ባለሙያው አክለዉም በአንዳንድ ሰዎች ላይ በጨጓራ ባክቴሪያ አማካኝነት ወደ ካንሰር የመቀየር ዕድል ሊኖረዉ እንደሚችል አስገንዝበዋል።ለህመም ማስታገሻ ተብለዉ የሚወሰዱ እንደ አይቡፕሮፌን እና አስፕሪን ያሉ መድሃኒቶች ለረጅም ጊዜ የሚወሰዱ ከሆነ ለጨጓራ ቁስለት ሊያጋልጡ ይችላሉ በማለት የህክምና ባለሙያው ጨምረው ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል።